በጎፋ ዞን ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬቾ ሻቻ ጎዝዲ ቀበሌ ነዋሪዎች ላይ በመሬት ናዳ ሳቢያ ሕይወታቸውን ያጡ ሰዎች ቁጥር በየዕለቱ እየጨመረ መጥቷል።
የአካባቢው ነዋሪዎች ለሞትና የመቁሰል አደጋ የተጋለጡት ሐምሌ 14 እና 15 ከፍተኛ ዝናብ ባስከተለው የመሬት ናዳ ነው።
የዞኑ መንግሥት ረዳት ተጠሪና የፖለቲካና የሕዝብ ግንኙነት ዘርፍ ኃላፊ፤ የአስቸኳይ አደጋ ጊዜ መልሶ መቋቋሚያ ዐቢይ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ኃብታሙ ፌተና ሐምሌ 16 በሰጡት መግለጫ የሟቾች ቁጥር 146 መሆኑ የተገለጠ ሲሆን፤ ሐምሌ 19 በአካባቢው ባለስልጣናት በተሰጠው መግለጫ መሠረት ሕይወታቸውን ያጡ ሰዎች ቁጥር 257 መድረሱ ተገልጧል።
በተጨማሪም የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብዓዊ ጉዳዮች ቢሮ ከአካባቢው ባገኘው መረጃ መሠረት የሟቾች ቁጥር 500 ሊደርስ እንደሚችልና ከ15000 ሺህ በላይ የአካባቢው ነዋሪዎችን ደህንነት ከቀጣይ የመሬት ናዳ ለመታደግ ከአደጋ ወደ ራቀ ሥፍራ ማሥፈር እንደሚያሻ አሳስቧል።
ከመሬት ናዳው አደጋ የተረፉት ወ/ሮ ፀጋነሽ ኦቦሌ እንደምን ከኮረብታ አሽቆልቁሎ የመጣው የጭቃ ናዳ ከስድስት ልጆቻቸው ጋር እንደዋጣቸው ለአዣንስ ፍራንስ ፕሬስ ሲናገሩ "ልጆቼን ጨምሮ ከሌሎች ሰዎች ጋር በጭቃ ናዳው ተውጬ ነበር።
"ወንድሜ ዳዊት ጭቃው ውስጥ ገብቶ አወጣኝ። አራቱ ልጆቼ ሞቱ። ተቀበሩ" ብለዋል።
ባለቤታቸው በሕይወት መኖራቸውና አለመኖራቸው እስካሁን አልተረጋገጠም።
የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ሐምሌ 16 በአራት ከባድ የጭነት መኪናዎች ሕይወት አዳኝ አቅርቦቶችን ይዞ በሥፍራው እንደተገኘ፣ የአካባቢው መንግሥትም ድጋፍ እየቸረ እንዳለና ዓለም አቀፍ ድርጅቶችም ትብብር በማድረግ ላይ እንደሚገኙ ተመልክቷል።